በአዲስ አበባ ከተማ በመጪው ክረምት ከ6 ሚሊዮን በላይ
ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ ነው ፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ በመጪው ክረምት ከ6 ሚሊዮን በላይ
ችግኞችን ለመትከል የቅድመ ዝግጅት ስራ መጠናቀቁን
በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የማዘጋጃ ቤታዊ ዘርፍ ስራ አስኪያጅ
አቶ ጥራቱ በየነ ገለጹ፡፡
አቶ ጥራቱ በየነ ከአዲስ አበባ ከተማ አካባቢ ጥበቃ እና
አረንጓዴ ልማት ኮሚሽን አመራሮች ጋር በመሆን በእንጦጦ፣
ጉለሌ እና ሱስኒ ችግኝ ጣቢያዎችን በመገኘት እየተደረገ
ያለውን ዝግጅት ተመልክተዋል፡፡
በጉብኝቱ የማዘጋጃ ቤታዊ ዘርፍ ስራ አስኪያጅ አቶ ጥራቱ በየነ
እንደገለጹት ባለፉት ሁለት አመታት በከተማዋ የተጀመረውን
የአረንጓዴ ልማትን መርሃግብርን ለማስቀጠል በተለያዩ ችግኝ
ጣቢያዎች ከ4 ሚሊዮን በላይ አገር በቀል እና የፍራፍሬ
ችግኞችን በማፍላት ስራ በመከናውን ላይ መሆኑን ተናግረዋል
።
በመጪው ክረምት በአዲስ አበባ ከተማ ደረጃ በመንግሥት
ችግኝ ጣቢያዎች እና በግል ችግኝ አልዎች በአጠቃላይ ከ6
ሚሊዮን በላይ ይተከላሉ ያሉት አቶ ጥራቱ ከዚህም ውስጥ 1.5
ሚሊዮን የሚሆኑት ለምግብነት የሚውሉ የጓሮ አትክልትና
ፍራፍሬ ችግኞች ናቸው ብለዋል፡፡
በባለፈው ክረምት በአዲስ አበባ ከተማ ደረጃ 8.2 ሚሊዮን
ችግኞች የተተከሉ ሲሆን ከ83 በመቶ በላዩ መጽደቃቸውን
የአዲስ አበባ ከተማ አካባቢ ጥበቃ እና አረንጓዴ ልማት ኮሚሽን
አስታውቋል፡፡
